.

.
ዋና ገጽ » » "የመነኮሳት ሕይወት"

"የመነኮሳት ሕይወት"

Unknown (በዲያቆን ንጋቱ አበበ) Saturday, December 20, 2014 | 12:23 AM


ምንም እንኳን የድንግልናና የምናኔ ኑሮ ቀደም ብሎ የተጀመረ ቢሆንም የምንኩስና መሥራችና አባት ቅዱስ እንጦንስ ነው፡፡ አባ እንጦንስ ግብፅ ውስጥ በምትገኝ ቆማ በምትባል ቦታ በ251 ዓ.ም ተወለደ፡፡ ወላጆቹ ሀብታሞችና ደጋግ ሰዎች ነበሩ፡፡ ከወላጆቹ ዕረፍት በኋላ የነበረውን ሀብት ለድሆች መጽውቶ መንኩሶ ብዙ ዓመት በብሕትውና ኖረ፡፡
በዚያን ጊዜ ብዙ ታምራትን ስለሠራ ሕዝቡ ግማሹ እሱን አይቶ ለማድነቅ የቀረው ደግሞ በእርሱ ጸሎት ለመፈወስ ወደነበረበት ቦታ ይጐርፍ ነበር፡፡ እርሱም በ356
ዓ.ም ዐረፈ፡፡


አባ ጳኩሚስ የተባለ ሌላው አባት በላይኛው ግብፅ ውስጥ ብዙ ገዳማትን በመሥራት የምንኩስናን ሕግና ሥርዓት በመወሰን ስለምንኩስና መስፋፋት ብዙ ደክሟል /290-347 ዓ.ም/፡፡ አንድ ቀን ወደ ዱር እንጨት ፍለጋ ሔዶ ሳለ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጸለትና እንደ አባቶቻችን ሐዋርያት የአንድነትን ማኅበር ለመሥራት መነኮሳትን እንዲሰበስብ አዘዘው፡፡ ብዙ አማኞች እየናፈቁት ማግኘት ያልቻሉትን ገዳማዊ ሕይወት ያገኙ ዘንድ ገዳም ለመመሥረት የሚስችለውንና የሚያስተዳድርበትን በነሐስ ላይ የተቀረጸ ሕግ ሰጠው፡፡ አባ ጳኩሚስም ከመልአኩ በተሰጠው ሕግ መሠረት የሚተዳደር ገዳም አቋቋመ፡፡ ይኸውም መነኮሳቱ ጠዋትና ማታ አብረው እንዲፀልዩ በአንድነት እንዲሠሩ ገቢና ወጪያቸው አንድ ላይ እንዲሆን በአንድነት እንዲመገቡ፣ ልብሳቸው አንድ አይነት እንዲሆንና እነዚህን የመሳሰሉትን ደንቦች አወጣላቸው፡፡ በዚህ መሠረት መነኮሳቱ የዕለት ምግባቸውን የሚያገኙት እየሠሩ ነበር፡፡ ከሴቶችም የምንኩስናን ሕይወት የጀመረች የአባ ጳኩሚስ እህት ማርያም ናት፡፡

ከዚህ በኋላ በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ጀምሮ ምንኩስና በግሪክ፣ በሮም፣ በሶሪያና በሌሎችም ሀገሮችም እየተስፋፋ ሄደ፡፡

የምንኩስናን ሕይወት ወደ ኢትዮጵያ ያመጡ በ5ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በጉባዔ ኬልቄዶን /በሃይማኖት ስደት/ ምክንያት ከቁስጥንጥንያ፣ ከግብፅ፣ ከሶርያ፣ ከሮም፣ ከአንጾኪያ ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ዘጠኙ ቅዱሳን መነኮሳት ናቸው፡፡ ምንኩስና ከተመሠረተ ጀምሮ በየጊዜው ሕዝቡ ታላላቆችም ሳይቀሩ ወደ ገዳማቱ እየሄዱ ይመነኩሱ ነበር፡፡
ነገር ግን ከ9ኛው መቶ ዘመን ጀምሮ በማኅበር ከሚኖሩት መነኮሳት መካከል ጥቂቶቹ ቀስ በቀስ ለብቻ በተለየ ቤት መኖር እያንዳንዱ መነኩሴ ለብቻ በፈለገበት ጊዜ መብላትና መተኛት ስለጀመረ በየገዳማቱ የመነኮሳቱ ኑሮ በማኅበር የሚኖሩትና ለብቻቸው የሚኖሩት ለሁለት ተከፈሉ፡፡

የድንግልና መሠረቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «ስለ መንግሥተ ሰማያት ሰውነታቸውን ጃንደረባ ያደረጉ አሉና፤ መፈጸም የሚችል ግን ይፈጽም» ሲል የተናገረው የሕግ ቃል ነው፡፡ ማቴ. 19፡12

ይቆየን.......

0 comments:

Post a Comment

Note: Only a member of this blog may post a comment.

ቤተልሔም ዘተዋሕዶ

በኦርቶዶክሳዊት
ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ ለሚነሱ ማንኛውም ጥያቄ መልስ
ለመስጠት የሚሰራ ብሎግ ነው። ያለዎትን ጥያቄና አስተያየት ይላኩልን።
ቅዱሳትመጻህፍትን አገላብጠን፤ አበው ሊቃውንትን ጠይቀን፤ ያገኘነውን
መልስ ወደእናንተ እናደርሳለን!!!

"የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳን ጸሎት ጋር ከመልአኩ እጅ በእግዚአብሔር ፊት ወጣ" ራዕ 8፤4

"የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳን ጸሎት ጋር ከመልአኩ እጅ በእግዚአብሔር ፊት ወጣ"       ራዕ  8፤4

አዘጋጅ፦ ዲያቆን ንጋቱ አበበ

አዘጋጅ፦ ዲያቆን ንጋቱ አበበ

ቤተልሔም ዘተዋሕዶን ላይክ በማድረግ በፌስቡክ ይከታተሉ

በሳምንት ጊዜ ውስጥ ብዙ የተነበቡ

.